2014 ጁን 1, እሑድ

እናቱ መፀዳጃ ቤት ጉድጓድ ውስጥ የከተተችው ህፃን ከሞት ተረፈ በሐረር ከተማ “ማሳደግ አልችልም” በሚል ሰበብ የወለደችውን ህፃን በፌስታል አድርጋ መፀዳጃ ቤት ጉድጓድ ውስጥ የከተተች እናት በቁጥጥር ስር የዋለች ሲሆን ህፃኑ ከ6 ሰዓት በኋላ ከጉድጓዲ ወጥቶ ህይወቱ ተርፏል፡፡ በሐረሪ ክልል በቀበሌ 19 ልዩ ስሙ አማሪሳ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ ነዋሪ የሆነችው የ20 ዓመቷ ወጣት፤ ባለፈው ሐሙስ ከሌሊቱ ስምንት ሰዓት ላይ የተገላገለችውን ህፃን በፌስታል አድርጋ መፀዳጃ ቤት ጉድጓድ ውስጥ እንደከተተችው የክልሉ ፖሊስ የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ ኮማንደር ጣሰው ቻለው ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡ ከጠዋቱ ሁለት ሰዓት ላይ ወደ ሽንት ቤት ያመራ ጎረቤት የህፃኑን ለቅሶ ሰምቶ ለፖሊስ መጠቆሙንና ህፃኑ በመፀዳጃ ቤቱ ጉድጓድ ውስጥ ተንሳፎ በህይወት መገኘቱን የህዝብ ግንኙነት ኃላፊው ገልፀዋል፡፡ በቀን ሥራ የምትተዳደረው እናት ቤቷ ውስጥ ተኝታ መገኘቷን የገለፀው ፖሊስ፤ ህፃኑን መፀዳጃ ቤት ውስጥ የከተተችው የማሳደግ አቅም ስለሌላት እንደሆነ በመናገር ድርጊቱን መፈፀሟን አምናለች ብሏል፡፡ህፃኑ በሐረር ከተማ በሚገኘው የህይወት ፋና ሆስፒታል በመልካም ጤንነት ላይ እንደሚገኝ ፖሊስ ጠቁሞ፤ እናትየው ምርመራ እየተደረገባት እንደሆነ ገልጿል፡፡ (Source Addis Adimas news paper)

2014 ኤፕሪል 7, ሰኞ

ሰበር ዜና- በጎንደር ከተማ የ3 ሽህ ሰዎች መኖሪያ ቤት ይፈርሳል!!

በጎንደር ከተማ በህገ ወጥ መልኩ ተገንብተዋል የተባሉ ከ3 ሺህ በላይ መኖሪያ ቤቶች ሊፈርሱ ነው፡፡ ቤቶቹ በተለምዶ የጨረቃ ቤት ናቸው በሚል ሰበብ የሚፈርሱ ሲሆን እንደ አንዳንድ አስተያዬት ሰጪዎች የቤቶቹ መፍረስ የቤት አልባ ሰዎችን ቁጥር ከፍ እንደሚያደርገው ያምናሉ፡፡ ብዙ ቤተሰቦችም እንደሚፈናቀሉ ይታመናል!! መንግስት ቤቶቻቸው የሚፈርስባቸውን ቤተሰቦች ችግር ከወዲሁ ሊያጤነው እንደሚገባ ማሳሰብ እንወዳለን፡፡

2014 ማርች 24, ሰኞ

አማላጅ ያልተገኘለት የኢትዮ ቴሌ ኮም ጉዳይ - Disconnecting the Future


ስሙን እና አርማውን ብቻ ቀይሮ በግብር ግን ወደ ኋላ እየተንቀሳቀሰ ያለ ተቋም እንደ ኢትዮቴሌኮም አይገኝም፡፡ አንድ ጊዜ የፈረንሳይ ሌላ ጊዜ ደግሞ የቻይና ኩባንያወዎች እየተፈራረቁበት የሚገኘው ኢትዮቴሌኮም አሁን አሁን በተለይም ከቅርብ ወራት ጀምሮ አገልግሎት እየሰጠ ነው ማለት የሚከብድ ይመስለኛል (ምናልባትም ከስለላ ስራው ውጭ)፡፡ በአፍሪካ አነስተኛ ደንበኞችን በብቸኝነት ይዞ ጥራት ያለው አገልግሎት መስጠት የተሳነው አንጋፋው ድርጅት ነው፡፡ በእድሜ ብዛት ለውጥ አቅቶታል፡፡ ጎረቤት አገራት በርካታ የቴሌ ኩባንያዎች አላቸው፡፡ ሱዳን ውስጥ ከአራት በላይ አገልግሎቱን የሚሰጡ ተቋማት አሉ፡፡ ሱዳኒ፣ አረቢ፣ ኤም ቲ ኤን ... ይጠቀሳሉ፡፡ በጸጥታው ዘርፍ እንኳ እየታመሰች ያለችው ጎረቤት ሀገር ሶማሊያ ሶምቴል፣ ቴሌሶም፣ ቴሌኮም፣ ኤም ቲ ኤን የሚባሉ አገልግሎት ሰጭ ተቋማት አሏቸው፡፡ ከኬንያ ጋር መወዳደር አይቻልም፡፡ ታዲያ ምንም አማራጭ በሌለበት ሁኔታ ይህ ተቋም ከዘመድ አዝማድ ሁሉ ሊያቆራርጠን ነው፡፡ ከሚያውቁት ሰው ሲደውሉ የማያውቁት ሰው ያነሰዋል፡፡ ይቅርታ ጠይቀው እንደገና ያንኑ ቁጥር ሲመቱት በመካከል ሙዚቃ ይገባብዎታል፡፡ ሙዚቃው እስኪጨርስ ከጠበቁት በራሱ ጊዜ ይዘገዋል፡፡ አሁንም ሌላ ዘመድዎ ጋር ቢደውሉ ጆሮ የሚያደነቁር ድምጽ ሊሰሙ ይችላሉ፡፡ ሌላ ሰው ጋ ሳይሰለቹ ከደወሉ ከብዙ ሙከራ በኋላ ‹‹ይቅርታ የደወሉለትን ደንበኛ አሁን ማግኘት አይችሉም›› የሚል ሰቅጣጭ ድምጽ ይሰማሉ፡፡ የዚች ሴቲዮ ድምጽ በስልክዎ ሲያሰለችዎት ስልክዎን ሊወረዉሩ ይችላሉ፡፡ በዚህ መካከል ሁለት ነገሮች ያልቃሉ፡፡ አንደኛው ገንዘብዎት ምንም ሳያወሩ ያልቃል፡፡ ሁለተኛው የሞባይሉ ባትሪ እንዲሁ ያልቃል፡፡ የኢትዮጵያ መብራት ሀይል እርሱም መብራቱን አጥፍቶት ከሆነ ለቀናት የተዘጋ ሞባይል ቀፎ ይዞ ለመዞር እንገደዳለን፡፡ እናም በዚህ አካሄድ በ2020 ኢትዮጵያውያንን ከዓለም ጋር ብቻ ሳይሆን ከኢትዮጵያውያን ጋር የሚቆራርጠን ይሆናል፡፡ አይበልብንና ሌባ ቢመጣ ወደ ፖሊስ ጣቢያ ከመደወል ሰወው መላክ ይቀላል፡፡ ስልክ እስኪደወል ወንበዴው የፈለገውን ማድረግ ይችላል፡፡ አማልዱን ብለን አማለጅ አንልክ በማን እንሂድበት!! የጃን ሆይን ሞዓ አንበሳ አርማ አስወግዶ ኔትወርኩንም ኖት ዎርክ (Network to Not-work) አደረጎት አረፈ፡፡ እንደባለፉት ዘመናት ሁሉ በፖስታ በኩል መላላክ ብቸኛው አማራጭ ሊሆን ነው፡፡ የፖስታ ቤት ባለስልጣን ማርኬቲንግ ክፍል አስቦበት ከሆነ በርከት ያሉ የፖስታ ቁጥሮችን እንዲሁም ቅርንጫፎቹን ማብዛት ያለበት ይመስለኛል፡፡ ቴሌኮም እንደሆን ከቀን ቀን እየሆነ ያለውን እያየነው ነው፡፡

2014 ማርች 22, ቅዳሜ

ሰበር ዜና – የማኅበረ ቅዱሳንን አመራርና አባላት በአክራሪነት የሚከስ ዶክመንተሪ ሊዘጋጅ ነው ተባለ


ዶክመንተሪው የ2007 ሀገራዊ ምርጫ ቅድመ ዝግጅት አካል እንደኾነ ተጠቁሟል ‹‹ማስረጃ አቅርቡና እንነጋገርበት›› ለሚለው የማኅበሩ ጥያቄ ምላሽ አልተሰጠም በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሲኖዶሱን ይኹንታ አግኝቶ በመላው አገሪቱ የሚንቀሳቀሰውን የማኅበረ ቅዱሳንን አመራርና አባላት በአክራሪነት የሚከስ ነው የተባለ ዶክመንተሪ ፊልም ለማዘጋጀት መታቀዱ ተጠቆመ፡፡ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ አንዳንድ ሓላፊዎች አቀብለውታል በተባለ መረጃ እንደሚታገዝና በመንግሥት አካል እንደሚሰናዳ የተገለጸው የዶክመንተሪ ዝግጅቱ በማኅበሩ ኻያ አመራሮች እና አባላት ላይ እንዳነጣጠረ ተገልጧል፡፡ መንግሥት በምርጫ – 97 ውጤትና በተከታይ ኹኔታዎቹ ላይ ባካሔደው ግምገማ፣ የማኅበረ ቅዱሳን አባላት ናቸው የሚባሉ ግለሰቦች በተለይ በገጠር ቀበሌዎች ለተቃዋሚዎች ተሰሚነት ማግኘት በምክንያትነት መጥቀሱ በዜና ጥቆማው የተመለከተ ሲኾን ‹‹የአክራሪነትና የጽንፈኛ ፖሊቲከኞች ምሽግ ነው›› በሚል የሚያቀርበው ክሥም ከዚኹ የሚነሣና ለመጪው የ2007 ሀገራዊ ምርጫ የሚደረግ ቅድመ ዝግጅትም አካል እንደኾነ ተነግሯል፡፡ በቅድመ ዝግጅቱ የሚወሰዱ ርምጃዎች የማኅበሩን አቅሞችና እንቅስቃሴዎች በመቆጣጠር በተለይም የማኅበሩ መሠረቶች ናቸው የሚባሉ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ግቢ ጉባኤያትን ‹‹በሴኩላሪዝም መርሖዎች የመግባቢያ ሰነድ›› ጠርንፎ ‹የአገልግሎት ቅኝቱን የማስተካከል› ዓላማ እንዳላቸው የገለጸው የዜና ምንጩ፣ ይህም ካልተሳካ በተከታታይ አስተዳደራዊ ርምጃዎችና የተቃውሞ ቅስቀሳዎች ማኅበሩን በማወከብ ተቋሙን ለዘለቄታው የማፍረስ ውጤት ሊኖረውም እንደሚችል አመልክቷል፡፡ ከአዲስ አበባ ሀ/ስብከት አብያተ ክርስቲያናት የተጠሩ ናቸው የተባሉ አስተዳዳሪዎችና ሠራተኞች የሚሳተፉበት እንደኾነ የተገለጸና ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ በማኅበሩ አገልግሎት ላይ ቁጥጥሩን እንዲያጠብቅ የሚጠይቅ ስብሰባ በዛሬው ዕለት በቤተ ክህነቱ የመሰብሰቢያ አዳራሽ እንደሚካሔድ የተዘገበ ሲኾን ዓላማውም ‹‹በአክራሪዎችና ጽንፈኛ ፖሊቲከኞች ምሽግነት፣ የቤተ ክህነቱን አሠራር ባለማክበርና ከቤተ ክህነቱ በላይ ገዝፎ በመውጣት›› ማኅበሩ የሚከሰስባቸውን ኹኔታዎች በማጠናከር ለታቀዱት ርምጃዎች የሚያመቻች ነው ተብሏል፡፡ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች ላይ በማተኮር የተማረው ትውልድ ሃይማኖቱን የሚወድ፣ ግብረ ገብነት ያለው፣ ሀገሩንና ቤተ ክርስቲያኑን በዕውቀቱ፣ በሞያውና በገንዘቡ የሚያገለግል ብቁ ዜጋ ይኾን ዘንድ በቅዱስ ሲኖዶስ ጸድቆ በተሰጠው መተዳደርያ ደንብ መሠረት በመሥራት ላይ እንዳለ የሚገልጹ የማኅበሩ አባላትና ደጋፊዎቹ፣ ማኅበሩ ለቀረቡበት ክሦች የሚመች አደረጃጀት ይኹን ባሕርይ እንደሌለው በመግለጽ ተጠሪ ከኾነለት ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጋራ በአሠራር ሒደት የሚፈጠር ክፍተትን በማጦዝ የሚሰነዘሩ ውንጀላዎች ተቀባይነት እንደሌላቸው ተናግረዋል፡፡ የተጠቀሱት ክሦች ላቀረቡት አካላት ‹‹የሚነገረውና የሚጻፈው እኛን የሚገልጸን ስላልኾነ ማስረጃ አቅርቡና እንነጋገርበት›› የሚል ጥያቄ ቢቀርብላቸውም ለሠለጠነ ውይይት ፍላጎት እንደሌላቸው አባላቱ አስረድተዋል፤ በምትኩ ‹‹ርምጃ እንወስዳለን›› በማለት በተለያዩ መድረኮች ማኅበሩን ማሳጣትና መክሠሥ እንደሚመርጡም ለፋክት መጽሔት አስታውቀዋል፡፡ ታቅዷል የተባለው የዶኩመንተሪ ዝግጅት እውነት ከኾነም ማኅበሩን ብቻ ሳይኾን የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን የማዳከም አጠቃላይ ዘመቻ አድርገው እንደሚቆጥሩትና በቀላሉ እንደማይመለከቱት አሳስበዋል፡፡ sources:(ፋክት፤ ቅጽ ፪ ቁጥር ፴፰፤ መጋቢት ፳፻፮ ዓ.ም.)

2014 ማርች 13, ሐሙስ

በሸንቁጥ አየለ የተደረሰዉ ኅቡእ ጣት (ዘ ሀይድ) መጽሀፍ ዕሁድ መጋቢት 7/2006 ዓም በሀገር ፍቅር ቲያትር ይመረቃል በሸንቁጥ አየለ የተደረሰዉ ኅቡእ ጣት (ዘ ሀይድ) መጽሀፍ ዕሁድ መጋቢት 7/2006 ዓም በሀገር ፍቅር ቲያትር ከጠዋቱ 3 ሰዓት እስከ 6 ሰዓት ይመረቃል:: በምርቃት ፕሮግራሙ ላይ ታዋቂ ሰዎች : ጋዜጠኞችና የስነ ጽሁፍ ባለሞያዎች ተገኝተዉ ስለ መጽሃፉ ያላቸዉን አስተያዬት ይሰጣሉ:: ኅቡእ ጣት (ዘ ሀይድ) መጽሀፍ ኢትዮጵያ በዉስጡዋና በዙሪያዋ ባሉ ልዩ ልዩ ስነልቦናዊ: ታሪካዊ : ፖለቲካዊ: ሳይንሳዊና ማህበራዊ ጭብጦች ዙሪያ የሚያጠነጥን መሆኑ ተገልጾአል:: ዙሪያዋን ያሉ ታላላቅ የሀገሪቱ ጠላቶች ኢትዮጵያ ፈርሳ ማዬት ትልቁ የቤት ስራቸዉ ብቻ ሳይሆን ከፍ ያለ ቅዱስ ተልዕኮአቸዉም መሆኑን የሚተርከዉ ይህ መጽሀፍ የሚያጠነጥነዉ የሀገሪቱ ባላንጣዎች ታላቁን የቤት ስራቸዉን ብሎም ቅዱስ ተልዕኮአቸዉን ለማሳካት በታላቅ ትጋት : በከፍተኛ ጥበብና በሙሉ ሀይላቸዉ ስራቸዉን ሲከዉኑ ያሳያል ተብሎአል:: ሀገሩ ያበሳቆለችዉንና የገፋችዉን ተራ ዜጎች ብሎም መንግስት ጆሮ አልስጥ ያላቸዉን ታታላቅ ሳይንቲስቶችን ጭምር ለዚህ ተልዕኮ ሊያሰልፉዋቸዉ ሲባትቱ የሚከተሉዋቸዉን ሂደቶች ልብ ሰቃይ በሆነ መልክ ያሳያል:: ይህ መጽሀፍ ሳይንስ በኢትዮጵያ ምድር ፍሬ እንዲያፈራ ከተፈለገ ባለ አዕምሮ የሀገሪቱ ዜጎች የሚሉትን በጥንቃቄ ማድመጥ ወሳኝ መሆኑን ለማሳዬት እንደሚሞክር ተገልጾአል:: የሀገሪቱ ብሄሮች ወደ ከፍተኛ ቅራኔና የእርስ በእርስ መጠፋፋት እንዲገቡ በመጨረሻም ሀገሪቱ ፍርስርሱዋ እንዲወጣ ሁሉንም አሉታዊ ድሮች የሚያደሩት የሀገሪቱ ባላንጣዎች ብርና ሀብታቸዉን በኢትዮጵያ ምድር እንደ ጉድ ሲያፈሱት የሚያሳይ ብሎም ስለላ : ንግድ እና ሸፍጥ ተጎናጉነዉ ሲጦፉ የሚተርክ መጽሀፍ መሆኑን ደራሲ ሸንቁጥ አየለ አብራርቶአል:: ሀገር ከሰራዊት በላይም የዜጎቹዋ ጥበቃ የግድ ያስፈልጋታል በሚል ጽኑ መርህ ላይ የቆመ መልዕክት ያለዉ ይህ መጽሀፍ የግብጽና የሌሎች ጎረቤት ሀገራት ኢትዮጵያን የማፍረስ ተልዕኮ በኢትዮጵያዉያን ዜጎች እንዲከሽፍ ከተፈለገ ከብሄረተኝነት ይልቅ ኢትዮጵያዊነት ብቸኛ መሳሪያ ነዉ የሚል ጥልቅ ይዘትን እንደሚያስተላልፍ ታዉቁአል:: በአጠቃላይ ኢትዮጵያ ባላት የዉሃ ሀብትና ሌሎችም ተያያዥ ሀብቶች ግብጽ ስታገሳ ኤርትራ ስትወናጨፍ ሌሎች ጠላቶች እያጨበጭቡ ኢትዮጵያ ያላትን ሁሉ ሊያሳጡዋት ቢዘጋጁም ኮሳሶቹ ኢትዮጵያዊ ዜጎች ግን ኢትዮያዊነትን እንደ ኒኩሊየር አረር ሲተፉ የሚተርክ መጽሀፍ መሆኑ ታዉቆአል:: 206 ገጽ ያለዉ ኅቡእ ጣት (ዘ ሀይድ) መጽሀፍ የሸንቁጥ አየለ ሁለተኛ የመጽሀፍ ስራዉ ሲሆን ከዚህ በፊት የጠፍ ከዋክብት የሚል መጽሀፍ ማሳተሙም ታዉቁዋል:: ደራሲዉ ከዚህ በተጫማሪም ማዕበል የሚል ፊልም ደርሶ ለህዝብ ማቅረቡና ልዩ ልዩ ጽሁፎችን በተለያዩ ሚዲያዎች ላይ ለአንባቢያን የሚያቀርብ መሆኑ ተገልጾአል:: ኅቡእ ጣት (ዘ ሀይድ) መጽሀፍ ከመጋቢት 7/2006 ዓም ጀምሮ በገበያ ላይ እንደሚዉል ደራሲዉ ገልጾአል::

2014 ማርች 11, ማክሰኞ

ግብረ ገብነት ሆይ ማደርያህ ከወዴት ነው? ክፍል ሁለት

ካንገት በላይ ስንስቅበት - የዘመኑ ጥርስ አረጀ፤ ሳቅ ራሱ ጥርስ ናፈቀ - ጥርስም ፈገግታን ጎመጀ፤ ምነው ሰው ሁሉ ሳቅ ራበው! ምነው ሰው ሁሉ ጥርስ አጣ! ቁም ነገር ዳዋ ለበሰ - ህይወት ሆነ የለበጣ! ጥርስ መሳቂያ ጊዜ አጣ - ማኘክ ብቻ ሆነ ስራው! ከልክ በላይ መብላት ለምዶ - ሆዳችን እያስፈራራው! የትውልድ ጥርስ ሻገተ - አጓጉል ስራ በዛበት! ያልሰራንበትን ጎርሰን - የሰው ላብ ስናኝክበት!!! (ግጥም በሞገስ ሀብቱ፤ የጋዜጠኛው ማስታወሻ የተወሰደ) **** ከላይ ያለው ግጥም ግሩም ነው፡፡ ጥርሳችን ፈገግታን ፈልጎ አጣ ይለናል፡፡ ፈገግታም በሙሉ ልቡ የሚስቅበት ጥርስ ፈለገ፡፡ ግን የት ይምጣ፡፡ የሚስቁት ጥርስ የላቸውም፡፡ ጥርስ ያላቸው ደግሞ ማኘክን እንጅ መሳቅ የማይችል /የተሳነው ሆነባቸው፡፡ ከአካላቶቻችን ሁሉ የአዛዥነትን ሚና የሚጫወተው ሆድ ሆነ፡፡ ጥርስም ጌጥነቱን አቆመ፡፡ የሰው ላብ ያለበት የቆሸሸ ነገር ሲያኝክ እንደ በረዶ ጸዓዳ የነበረው ጥርስ ወየበ፡፡ ህሊናም ማሰቡን ትቶ ዙፋኑን ለሆድ ለቀቀ፡፡ ግብረ ገብነትም ከህሊና ጋ አብሮ ጠፋ፡፡ ህሊና ገልብጦ ማንበብ የጀመረለት ግብረ ገብነትም ይገለበጣል፡፡ ባለፈው ሳምንት ካቆምንበት ወሬ አልወጣሁም፡፡ ዛሬም ግብረገብነት ሆይ የት ነህ እያልኩ ነው፡፡ ግብረ ገብነትን በስም ሳይሆን በግብር ፍለጋ እየማሰንሁ ነው፡፡ በቤተሰብም በተቋምም፣ በግልና በቡድን፣ በተማረውና ባልተማረው፣ በሊቁም በደቂቁም፣ በአለቃውም በምንዝሩም፣ በገዢውም በተገዥውም በር ላንኳኳ ነው - ግብረ ገብነት ካለ በማለት፡፡ ድምጼን ከፍ አድረጌ ‹‹ግብረ ገብነት ሆይ ከቶ ከወዴት ነህ!›› እየተጣራሁ ነው፡፡ በየመስሪያ ቤቱ በር ደርዘን ያክል የሥነ ምግባር መርሆዎች ተጽፈው ባየሁበት ቢሮ አቅጣጫ ሁሉ አንኳኳው፡፡ ስማቸው ብቻ እንደ ሙት መታሰቢያ ሀውልት/ ፎቶ ተሰቅሎ አንድም እንኳ ማገኘት ተሳነኝ፡፡ እናም ዛሬ የ12ቱ ስነ ምግባር መርሆዎች አሉበት በተባለው ቦታ ሁሉ ዞሬ ያገኘገሁትን እና የደረስኩበትን የምርመራ ውጤት እንዲህ ሪፖርት ላቀርብ ወደድኩ፡፡ 1. የመንግስት የግዥ ሂደት፡ የግዥ የስራ መደብ ላይ ለመቀጠርና ለመስራት በጣም እድለኛ መሆንን ይጠይቃል፡፡ አሁን በቃ ግልጽ ነው፡፡ ግዥ የስራ መደብን በሀላፊነት ሳይሆን ባበለሙያነት መቀጠር ሎተሪ ከማሸነፍ የላቀ ነው፡፡ ግዥ የስራ መደብ ላይ የሚሰራ ሰው ወዳጁ ብዙ ነው፡፡ በዓመቱ እርሱም የመስሪያ ቤቱን ፍላጎት በማየት ራሱ አቅራቢ ድርጅት ይከፍታል - ይሉኝታ ያለበት በዘመዱ አሊያም በቤተሰቡ አይን ያወጣው ደግሞ በራሱ ስም፡፡ እቃ አቅራቢው ድርጅት ጋ መደራደር በጣም የተለመደ ነው፡፡ ግዥው በቀጥታ፣ በውስንና በግልጽ ጨረታ ሊካሄድ ይችላል፡፡ በቀጥታ ከሆነ ከምትፈልገው ባለሀብት ጋ ትሄዳለህ፡፡ ባለሀብችም ይጠይቃሉ - ‹‹ግዥው በመስሪያ ቤት ነው!›› የመስሪያ ቤት ዋጋ ከፍ ይላል፡፡ ትርፉ ከሁለት ይገመሳል፡፡ ‹‹ላምጪው እንዲከፈል ህግ ያስገድዳል›› ይላሉ የኮሚሽን ሲከፍሉ፡፡ ጀማሪ ገዥ ከሆነ በመጀመሪያው የሰጡትን ይቀበላል፡፡ ልምድ ያለው ባለሙያ ከሆነ ደግሞ ይከራከራል፡፡ ‹እንዴ ይኸ ለኔ ያንሳል፤ ወዳጅነታችንን ማሰብ አለብህ!›› ብሎ አቤቱታ ያቀርባል፡፡ ወይም ደግሞ መተሳሰብ ይጀምሩና የሂሳብ ሊቅ ሊቀጥሩም ይችላሉ፡፡ ባለሀብቱም የሚመጣውን ጊዜ በማሰብ ሳያቅማማ ይከፍላል፡፡ በተሻሻለው የመንግስት የግዥ ደንብ መሰረት አንድ መስሪያ ቤት እንደ ደረጃው ከግማሽ ሚሊዮን ብር በላይ ግዥ በአንድ አመት በቀጥታ ግዥ ሊፈጽም ይችላል፡፡ በአንድ ጊዜ ደግሞ እስከ 50 ሺህ ብር ድረስ በአማካይ መግዛት እንደሚቻል መመሪያው ያዛል፡፡ በፕሮፎርማ ተሰብስቦ የሚገዛ ከሆነ ድግሞ አንዱን የምትግባባውን ባለሀብት ትመርጣለህ፡፡ ሶስት የዋጋ መሰብሰቢያ ቅጾችን ትሰጠውና ዋጋውን ሞልቶ በተለያየ ማህተም እና ንግድ ፈቃድ በፖስታ አሽጎ ይመልሳል - በለሀብቱ፡፡ አንዳንድ ጊዜ ደግሞ ዋጋውን ራሱ የግዥ ባለሙያው ሞልቶ በፓስታ አሽጎ ማህተም ብቻ ለማስረገጥ ይሰጠዋል፡፡ ባለሀብቱ የተባለውን ያደርጋል - ግዢው በዚህ መልኩ ይፈጸማል፡፡ በግልጽ ጨረታ የሚካሄዱ ግዢዎች ትንሽ ወሰብሰብ ይላሉ፡፡ እርግጥ ነው ጠቀም ያለ ጉርሻ ያለውም ከዚሁ ግዥ ላይ ነው፡፡ አንዳንዴ ብዙ ሰዎችን ያነካካል፡፡ አሁን አሁን ተጫራቾችም አስቀድመው አለውህ ያላቸው ሰው ከሌለ በስተቀር የጨረታ ሰነድ አይገዙም፡፡ ቢገዙም ሰው ከሌላቸው እንደማያሸንፉ ያውቃሉ፡፡ ጨረታው የተከፈተ እለት የዋጋው ዝርዝር ታይቶ አሸናፊው በሌላ ቀን የሚነገርበት ጊዜ አለ፡፡ አንዳንድ ጊዜ ድግሞ ጨረታው ሳይወጣ እንደወጣ ሆኖ አሸናፊው የሚነገርበትም ጊዜ አለ፡፡ እቃው ሳየይገዛ እንደተገዛ የሚሆንበት ጊዜም አለ፡፡ አላስፈላጊ ግዢዎችም ተገዝተው አገልግሎት ሳይሰጡ እቃዎቹ የሚበላሹበት ጊዜም አለ፡፡ በመስሪያ ቤቱ ሀላፊ ስምም የሚገዙበት አጋጣሚም አለ፡፡ እንዲያውም አንድ የክልል ባለስልጣን የነበረ በሀላፊነት ሲመራው በነበረው መስሪያ ቤት ውስጥ አንድ ቡልዶዘር በስሙ በእርዳታ ይሁን በግዥ በስሙ ገቢ ይሆናል፡፡ እናም ይህን ግለሰብ የክልል ቢሮ ሀላፊ መሆኑ አልበቃውም በማለት የሀይለ ማርያም መንግስት የሚኒስተርነት ማዕረግ እድገት ሰጠው ሲባል ሰምቻለሁ፡፡ የአግልግሎት ዘመናቸው ያለፈባቸው እቃዎችም የሚገዙበት ጊዜ አለ፡፡ በተለይ መድሀኒት ከሆነ ደግሞ አደጋው የከፋ መሆኑ እየታወቀ የሚገዛው ሰው ምን አይነት አዕምሮ ቢኖረው ነው ያስብላል፡፡ በቃ ለሰው ልጅ ገንዘብ ብቻ ዘመዱ የሆነ ይመስላል፡፡ ለማንኛውም ከዚህ ቤት ግብረ ገብነትን አጣሁት፡፡ ግብረ ገብነት ሆይ የት ነህ! ሌላ 12 የስነ ምግባር መርህ የተጻፈበትን ታፔላ አየሁ፡፡ ከዚህ ቤትም ገባሁ፡፡ እንዲህም አገኘውት፡፡ 2. የህንጻ ጨረታዎችን በተመለከተ ብዙ ጊዜ ግንባታዎችን የሚያካሂዱ መስሪያ ቤቶች ገማች መሀንዲስ አካተው ኮሚቴ ያቋቁማሉ፡፡ ተቋራጩ ከመሀንዲሱ ግምት በአስር በመቶ ከፍ እና ዝቅ ብሎ ዋጋ በማቅረብ ሊያሸንፍ ይችላል፡፡ በጣም ዝቅ ካለ አቅም የለውም፤ በጣም ከፍ ካለ ደግሞ የተጋነነ በሚሉ ምክንያቶች ውድቅ ይሆናል፡፡ ገማች መሀንዲሱ የግንባታውን ዋጋ ለመገመት በመጀመሪያ ከሚፈልጋቸው ተጫራቾች ጋር ውሳኔ ያሳልፋል፡፡ በህንጻ ጨረታ ማፈን የምትባል ነገር አለች፡፡ የመሀንዲሱን ግምት ተቋራጩ አስቀድሞ እንዳወቀ ሁለት ወይንም ሶስት ጨረታዎች በተለያዩ ፈቃዶች በስም በታሸገ ኢንቬሎፕ ይቀርባል፡፡ አንደኛው የመሀንዲሱን ግምት የመጨረሻ ዋጋ የያዘ፣ ሁለተኛው ደግሞ የመሀንዲሱን ግምት ከፍተኛ ዋጋ የያዘ ሌላኛው ደግሞ መካከለኛ ይሆናል፡፡ ስለሆነም በመካከል ሌላ ተቋራጭ አለመግባቱ ከታወቀ ሁለቱ አሊያም አንዱ በፈቃዱ ከጨረታ ውጭ ይሆናል፡፡ በሲፒኦ ያሳዙት ገንዘብ ከሚገኘው ትርፍ ጋር ሲነጻጸር አናሳ ስለሚሆን ገንዘቡ ገቢ ይሆንና ጨረታው በከፍተኛው ዋጋ ይሆናል፡፡ በዚህ ብቻ አያበቃም፡፡ የህንጻው ጥራት እንዲሁ ይሆናል፡፡ ከልዩ ልዩ ነገሮች ላይ ማጭበርበር ይፈጠራል፡፡ የሲሚንቶውና የጠጠሩ ውህደት መጠን፣ የብረቱ ጥንካሬና ውፍረት፣ መስታዎቶቹ፣ ጅፕሰሙ፣ ቀለሙ… ሁሉም በተገኘው ክፍተት ሁሉ እንደነገሩ ይሆናሉ፡፡ በጣም ቀላል ወጭ የሚያስወጣውን ውሃ እንኳን በደንብ ማጠጣት አይታሰብም፡፡ ህንጻውም አንድ አመት ሳይቆይ አገልግሎት መስጠት ሊያቆም ይችላል፡፡ መንገድም ከሆነ አንድ አመት ሳያገለግል ይፈራርሳል፡፡ በቅርቡ እንኳ በአዲስ አበባ በአንደኛው ሆስፒታል ብዙ ሚሊዮን ብር ተከፍሎት የታደሰው ሆስፒታል አንድ ክረምት እንኳ ሳያገለግል መበላሸቱን በኢቲቪ አይናችን ፕግራም ስንመለከት የዚህን ቤት ግብረ ገብነት አሳሳቢ ያደረገዋል፡፡ አንድ እየተደጋገመ የሚወራ ነገር አለ፡፡ ነገሩ ቀልድ ቢመስልም እውነት ሳይሆን አይቀርም፡፡ ችግሩ የተፈጠረው ገነት ዘውዴ የትምህርት ሚኒስተርነቷን ልትለቅ አካባቢ ነው፡፡ በዪንቨርሲቲዎች የህንጻ ማስፈፊያ ጊዜ አንድ ክፍለ ሀገር ያለ ዩንቨርሲቲ ስድስት ህንጻዎችን አስገነባው ብሎ ሪፖርት ያቀርባል፡፡ በስራ ላይ ጉብኝት ጊዜ አንደኛው ጠፋ ተባለ፡፡ የዩንቨርሲቲው ባለስልጣናትም እንደማያውቁ አብረው ከእንግዶች ጋር ፍለጋ ያዙ፡፡ በመጨረሻ ቦሌ አካባቢ ቆሞ ተገኘ የሚል ቀልድ ይሁን እውነት ሰምቻለው፡፡ እንደ እውነታው ብዙ ባለሀብቶች ተቋራጭነትን የሚመርጡት የምህንድስና ባለሙያ ስለሆኑም፣ ትርፉም ጠቀም ያለ ስለሆነ ብቻ አይመስልም፡፡ ምክንያቱም ብዙዎቹ ተቋራጮች መሀንዲስ አይደሉም፡፡ ይልቁንም ከዚህ ቤት ብዙ ማጭበርበር ስለሚቻል እንጅ፡፡ በአጼው ዘመን የተሰሩ ህንጻዎች ለታሪክ ማህደርነት ወደፊትም ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ አሁን አሁን ግን የሚሰሩ ህንጻዎች የገንዘብ ፍቅርና አለመታመን ተጨማምረውበት ሁለት አስርት አመታትንም መድፈን አስቸጋሪ እየሆነ ነው፡፡ በተለይ በመንግስት የሚገነቡ ተቋማት ጉዳይ አሳሳቢ ነው፡፡ ጤና ጣቢያዎች፣ ትምህርት ቤቶች፣ ዩንቨርሲቲዎች፣ ቢሮዎች፣ አውራ መንገዶች … እነዚህ ሁሉ የጥራት ችግር ያለባቸው ናቸው፡፡ በዚህ ሰፈር ከአስራ ሁለት ምግባር አንድም ጠፋ፡፡ ታማኝነት፣ ቅንነት፣ የህዝብ አገልጋይነት…፡፡ አይገርምም!! ግብረ ገብነት ሆይ የት ነህ!! አሁንም ሌላ ‹‹ደንበኛ ንጉስ ነው›› የሚል ጽሁፍ የተሰቀለበት ቢሮ እያዘገምኩ ነው፡፡ በር አካባቢ ‹ግብርን በመክፈል የህዳሴ ጉዟችንን እናፋጥን› የሚል ባነር በር አካባቢ ያየሁበት ቤት ነው - ገቢዎችና ጉምሩክ፡፡ 3. ገቢ ግብር መጽሀፍ የቄሳርን ለቄሳር የእግዚአብሄርን ለእግዚአብሄር ይላል፡፡ በዚህም የሰራ ሁሉ እንደገቢው ግብር ይጣልበታል፡፡ መንግስት ሰራተኛው ከደመወዙ ላይ ይወሰዳል፡፡ ችግሩ ያለው ከነጋዴው ነው፡፡ ነጋዴ ልዩ ግብር ይጣልበታል - በመንግስት፡፡ በስራውም በሚያስወጣቸውና በሚያስገባቸው ሸቀጦችም እንዲሁ፡፡ አንደ ሰው ገቢዎችና ጉምሩክ ስራ ከገባ ‹የእንኳን ደስ አለህ› መልዕክት የሚመጣው ከብዙ አጃቢዎቹ ዘንድ ነው፡፡ በተለይ በሚገቡና በሚወጡ እቃዎች ላይ ያለው ማጭበርበር ቀላል እንዳልሆነ በአይንም የምናየው በሀሜትም የምንሰማው ነው፡፡ ከፍተኛ ባለስልጣኖቻችንም በዚህ ዓመት ቃሊቲ የወረዱት በዚሁ አይደል!! ገቢዎችና ጉምሩክ የሚሰሩ የነበሩ አሁን የናጠጡ ባለሀብች ሆነዋል፡፡ በክልል ገቢዎች የሚሰበሰቡ የስራ ግብር በቁርጥና በስሌት ለመጣል ሲታሰብ አሁንም ከላይ ካየናቸው የተለየ አይደለም፡፡ የግብር ግምት እና ክትትል ባለሙያዎቹ፣ የስራ ሂደት መሪው፣ ኦዲተሩ ሁሉም እነርሱ እንዳደረጉት ይሆናል፡፡ ባለሀብቱ ከባለስልጣኑ ጋር ከተስማማ በሚሊዮን የሚከፍለው ወደ ሽዎች ዝቅ ይደረግለታል፡፡ ባለሙያው በጎን በኩል የባለ ሀብቱ የግል ሂሳብ ሰራተኛ ይሆንና ከታክስ እንዴት ማምለጥ እንደሚችል ይሰራለታል፡፡ ይህን ያደረገው ባለሙያም ለስራው ይሸለማል፡፡ በቃ ሂዎት እንዲህ ነች፡፡ የገቢ ክትትል ባለሙያው የተሳሳቱ መረጃዎችን ለግብር ገማቹ ባለሙያ ያቀብላል፡፡ የግብር ገማቹ ባለሙያ ደግሞ ከገቢ ክትትል ባለሙያው የሚመጡትን መረጃዎች ያድበሰብሳቸዋል፡፡ ኦዲተሩ ከሁሉም የተዘለሉትን እርሱም ይዘላቸዋል፡፡ የስራ ሂደት በለሙያውና የቢሮው ሀላፊ ደግሞ ከፍተኛ ግብር ከፋዮችን ይከታተልና እንደሚሆን ያደርጋል፡፡ በጣም የሚያሳዝነው ዝቅተኛ ገቢ ያላቸውና በችርቻሮ የሚተዳደሩ ሰዎች የንግድ ድርጅት በጥቃቅን ስህተት ሊታሸግ ሲችል ከፍተኛ ገቢና ትልቅ ድርጅት ያላቸውን ሰዎች ግን ከጥቃቅን ባለሀብቶች ላይ እንደፈለገ የማድግ ስልጣን የነበረው ባለሙያው የመናገር ስልጣን የለውም፡፡ ገንዘብ አሊያም ባለስልጣን ዘመድ ያለው በለሀብት የፈለገውን ያደርጋል፡፡ ቫት ሊያጭበረብር፣ ገቢው ሊደብቅ ይችላል፡፡ ፍርድ ቤት ሌባ እስካላለህ ድረስ በየትም የተገኘ ገንዘብ ይሁን ሀብትህ ነው፡፡ ባለሀብቱም፣ ባለሙያም፣ ባለስልጣኑም ተባብረው ለመንግስት ገቢ የሚሆነው ገንዘብ ይወስዱታል፡፡ መንግሰት መንግስትን ይሰርቃል፤ ህዝብ ህዝብን ይሸውዳል፡፡ የዚህ ቤት ገብረ ገብነት ይህ ነው፡፡ የተባለውን ላለመክፈል ያቅማማ ባለሀብት አገር ካልቀየረ በስተቀር መስራት አይችልም፡፡ ውሃ በቀጠነ ማስፈራሪያ ይደርሰዋል፡፡ እርግጥ ነው የተሰበሰበውም ገንዘብ አግባብ ላይ ይውላል ማለት አይቻልም፡፡ ግን በየቦታው ይመዘበራል፡፡ ታዋቂው የስነ ጽሁፍ ሰው ሸክስፒር እንዲህ አለ፡ ምናልባት ገንዘብ እድሜን አያራዝም ይሆናል፣ አሊያም እርሱ ያልደረሰበት ፍልስፍና ነው፡፡ ሸክስፒርም ይቀጥል፡ Life is cycle which turns on the wheel Starts on the womb ends on the tomb If life is a thing which money would buy The rich will live and the poor will die But nature in its wisdom made it too The rich and the poor together must go!! አይ እግዚአብሄር ደጉ ሀብታምንም ደሀንም አንድ ማድረጉ በጀን፡፡ እንጅማ!! ሰው የገንዘብ ባሪያ ሆነ ማለት ይህ ነው፡፡ በየትኛውም በኩል ይምጣ ብቻ ገንዘብ ይሁን፡፡ የሰው ህይወትም ለውጥ ይሁን፡፡ አዎ ገንዘብ ገንዘብ ገንዘብ፡፡ የዚህ ትውልድ አደገኛ አካሄድ ፍቅረ ንዋይ ነው፡፡ ግብረ ገብነት ከዚህ ቤት አጣሁት አሁን ፍለጋውን እቀጥላለሁ፡፡ አንድ ቀን አንድ ቦታ ላገኘው እችላለሁ ብየ ተስፋ በማድረግ፡፡ በሚቀጥለው ሳምንት ሌላ ቤት አንኳኳለው፡፡ እስከዚያው መልካም ሳምንት!! ይቀጥላል!! ሰላም

2014 ማርች 10, ሰኞ

ጉድ በል ጎንደር- ‹የመለስ ካምፓስ› በጎንደር ዩንቨርሲቲ!!

አስታውሳለሁ በ1999 ዓ.ም. የጎንደር ዩንቨርሲቲ አንደኛው ካምፓስ ስም ይሰጠው ተባለ እና ተማሪው ሁሉ ተወራከበ፡፡ ከማራኪ ካምፓስ በታች በኩል ያለው ካምፓስ ስያሜ ብዙ አጨቃጨቀ፡፡ ከዚያም ተማሪዎች ፊርማ አሰባሰቡ- አጤ ቴዎድሮስ ካምፓስ ይባል ተባለ፡፡ ከዩንቨርሲቲው አመራሮቸች ጋ ‹‹የነፍጠኛ ስም›› ነው የሚል ቅራኔ ቢኖርም በጊዜው ከነበረው የፖለቲካ ትኩሳት አንጻር ያን ስያሜ መቃወም ማለት አላስፈላጊ ብጥብጥ መፍጠር ነበር - እናም ስያሜው ጸደቀ፡፡ የከተማ ታክሲዎች አንዳች አገራዊ ፋይዳ ያለው አዋጅ እንደታወጀ በመቁጥር ‹‹አጼ ቴዎድሮስ ካምፓስ›› የሚል ወረቀት ጽፈው በጣም አስተዋወቁት፡፡ ከዚያ በኋላ ጎንደር ተረት የሆኑ ነገስታቶቿን ለማስታዎስ ይመስላል አሁንም ሌላኛውን ካምፓስ ‹‹ፋሲል›› ካምፓስ ተባለ፡፡ ከአመታት በኋላ ደግሞ ከከተማው ወጣ ብሎ ሌላ ካምፓስ ተገነባ፡፡ ይህ ካምፓስ ከከተማው ትንሽ ወጣ ያለ በመሆኑ ከተማሪ ትክተት ውጭ ነው፡፡ የዚህን ካምፓስ ስያሜ ለማውጣት ግን ተሜን ማማከር እንደቀድሞ አስፈላጊ አልነበረም፡፡ ከዩንቨርሲቲው ሴኔት ይሁን ከፌደሬሽን ምክር ቤት በተላለፈ ውሳኔ ‹‹መለስ ካምፓስ›› ተባለና በቅርቡ ተመረቀ፡፡ ግልጽ መሆን የነበረበት ለምን መለስ መባል እንዳስፈለገው ነው፡፡ መለስ በየሀገሩ ሁሉ ብዙ ቦታ ተሰይሞለታል፡፡ ‹መለስ ፓርክ፣ መለስ ሆስፒታል፣ መለስ ትምህርት ቤት፣ መለስ ጤና ጣቢያ፣ መለስ....› ብዙ መለስ የሚባሉ ቦታዎች ከከጋምቤላ እስከ ቶጎጫሌ፣ ከዛላንበሳ እስከ ሞያሌ ድረስ አሉ፡፡ በሁሉም አቅጣጫ ቢያንስ በአማካይ 10-20 ኪሌ ሜትር ርቀት ያለማጋነን በመለስ ስም የተሰየመ ነገር አይታጣም፡፡ በአማካይ 10-20 ጫማ ርቀት ደግሞ ስለ መለስ ራዕይ የሚሰብክ ሰው አይታጣም፡፡ ይህ ሆኖ ሳለ ስለምን ዩንቨርሲቲውን መለስ አሉት ቢባል መለሱ ግራ ያጋባል፡፡ ምናልባትም ‹መለስ የተማረ ሰው ስለሚወዱ› የሚል ካለ ተሳስቷል፡፡ ምክንያቱም በመጀመሪያ ከደደቢት በረሃ አራት ኪሎ ሲደርሱ አቶ መለስ ያደረጉት ነገር ቢኖር 44 በላይ ‹‹አሉ የተባሉትን›› የሀገሪቱን ምሁራንና ተመራማሪዎች ነው ድራሽ ያጠፋቸው፡፡ (በዚህ ሰዓት ከአዲስ አበባ ዩንቨርሲቲ የተባረሩ ሰዎችን ዝርዝር እያየሁ ነው ያሰብኩት፡፡) ተያይዞም የጎንደር ዩንቨርሲቲ ምክትል ፕሬዚዳንት መለስ ከሞቱ ቀደም ብሎ በመኪና አደጋ ህይወቱ ሲያልፍ ሌላው ለጎንደር ህዝብ አጠያያቂ አሟሟት ነበር፡፡ ምናልባትም አሁን በጎንደር አንድ ካምፓስ የተጀመረው ስያሜ አዲስ አበባ ባሉት ሁለት ዩንቨርሲቲዎችም አንደኛውን ሙሉ በሙሉ ዩንቨርሲቲው ‹‹መለስ ዩንቨርሲቲ›› ሊባል እንደሚችል ከወዲሁ መገመት አያዳግትም፡፡